የኬንያው የጤና ሚኒስትር የኢቦላ ለይቶ ማቆያ ማዕከል ግንባታ እንዲቆም ወሰኑ

የፎቶው ባለመብት, EPA
የኬንያ የጤና ሚኒስትር ኤደን ዱአሌ በአሜሪካ የሚደገፈው አወዛጋቢው የኢቦላ ለይቶ ማቆያ ማዕከል ግንባታ እንዲቋረጥ ውሳኔ አሳለፉ።
ሚኒስትሩ ውሳኔውን ከማሳወቃቸው ከአንድ ቀን በፊት ፍርድ ቤትን በመድፈር ጥፋተኛ መባላቸው አይዘነጋም።
ዛሬ ማክሰኞ ፍርድ ቤት የቀረቡት ሚኒስትሩ ይቅርታ ጠይቀው በኛኙኪ ግዛት በሚገኝ ወታደራዊ ሰፈር የሚገነባው የኢቦላ ለይቶ ማቆያ ማዕከል “በአፋጣኝ እና ሙሉ በሙሉ እንዲቆም” ማዘዛቸውን አስታውቀዋል።
ባለፈው ወር የመብት ተሟጋች ቡድኖች ያቀረቡትን አቤቱታ ተከትሎ የኬንያ ፍርድ ቤት 50 አልጋዎች ያሉት የለይቶ ማቆያ ማዕከል ግንባታ እንዲቆም ውሳኔ አሳልፏል።
ሆኖም ግን ሰኞ ዕለት የዋለው ችሎት የጤና ሚኒስትሩ ትዕዛዝ ችላ ብለው ግንባታው እንዲቀጥል በመወሰናቸው ፍርድ ቤትን በመድፈር ጥፋተኛ ብሏቸዋል።
ማዕከሉ በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በተቀሰቀሰው የኢቦላ ቫይረስ የተጠረጠሩ አሜሪካዊያን ለይቶ ማቆያ እንዲሆን ታስቦ ነበር።
የጤና ሚኒስትሩ ኤደን ዱአሌ “ድርጊቴ፣ ችላ ባይነቴ፣ አለመረዳቴ ወይም የተዛባ ግንዛቤዬ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ እንዳላከብር በማድረጉ ይቅርታ እጠይቃለሁ” ብለዋል።
የከፍተኛው ፍርድ ቤት ዳኛ ፓትሪሽያ ናዩንዲ የሚኒስትሩን ይቅርታ ተቀብለው “በጥብቅ ማስጠንቀቂያ” አሰናብተዋቸዋል።
የኢቦላ ለይቶ ማቆያ ማዕከል ግንባታ በኬንያውያን ዘንድ ቁጣ እና ተቃውሞ አስነስቷል። ፖሊስ ተቃዋሚዎችን ለመበተን ሲሞክር ሦስት ሰዎች ተገድለዋል።













