ቀጥታ, ኢራን የአሜሪካን ጥቃት የተኩስ አቁሙ “ከባድ ጥሰት” ስትል አወገዘች

ኢራን፣ አሜሪካ የፈጸመችውን አዲስ ጥቃት የተኩስ አቁሙ ”ከባድ ጥሰት” ስትል አወገዘች። የአሜሪካ ጦር በደቡብ ኢራን የሚገኙ የሚሳዔል ማከማቻዎች እና ፈንጂ የሚጥሉ ጀልባዎችን ዒላማ በማድረግ አዲስ ዙር ጥቃት መክፈቱን አስታወቋል። የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመግለጫው አሜሪካ “ጠብ አጫሪ እና ተቀባይነት ለሌለው ድርጊቷ” ተጠያቂ ትሆናለች ብሏል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኢራን ለሦስት ወራት ተቋርጦ የነበረው የኢንተርኔት አገልግሎት ተጀመረ

    በኢራን ለሦስት ወራት ያህል ተቋርጦ የቆየው የኢንተርኔት አገልግሎት ዳግም መጀመሩን የአገሪቱ ምክትል ፕሬዚዳንት አስታወቁ።

    ሞሃማድ ሬዛ አረፍ ማክሰኞ ዕለት በኤክስ ገጻቸው ላይ “ነጻ እና ቁጥጥር የሚደረግበት የኢንተርኔት አገልገሎት ለመስጠት የመጀመርያ እርምጃ ወስደናል” ብለዋል።

    ኔትብሎክስ እና ኬንቲክ የተባሉ የዓለም አቀፍ የኢንተርኔት ግንኙነትን የሚከታተሉ ተቋማት በኢራን ዛሬ ከምሳ ሰዓት ጀምሮ “በከፊል” የኢንተርኔት አገልግሎት መጀመሩን ተናግረዋል።

    በኢራን የኢንተርኔት አገልግሎት የተቋረጠው አሜሪካ እና እስራኤል የካቲት 21 2018 ዓ.ም. በአገሪቱ ላይ ጦርነት መክፈታቸውን ተከትሎ ነበር።

    የኢራን ባለሥልጣናት በጦርነቱ ወቅት ኢንተርኔት የተዘጋው ከደኅንነት ጋር በተያያዙ ምክንያት እንደሆነ ይናገራሉ። ይህንን በማድረግ ክትትል፣ ስለላ እና የሳይበር ጥቃቶችን ለመከላከል እንዳሰቡ ጠቁመዋል።

    በቴህራን የሚገኝ አንድ ግለሰብ ዛሬ የዋይፋይ አገልግሎት መጀመሩን ለቢቢሲ ተናግሯል።

    ኔትብሎክስ የኢንተርኔት አገልግሎት “የሚቀጥል” ስለመሆኑ “ግልጽ አይደለም” ብሏል።

  2. እስራኤል በሊባኖስ መንደሮች ላይ በፈጸመችው ጥቃት አስራ አንድ ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ

    እስራኤል በሄዝቦላህ ላይ የምትወስደውን ወታደራዊ እርምጃ እንደምታጠናክር ከገለጸች በኋላ በደቡብ እና ምሥራቃዊ ሊባኖስ በርካታ ድብደባዎችን መፈጸሟ ተገለጸ።

    የእስራኤል ጦር ከ100 በላይ የሄዝቦላህ መሠረተ ልማቶችን እና ተዋጊዎች ላይ የአየር ድብደባ መፈጸሙን ተናግሯል።

    በሚያዚያ ወር አጋማሽ ላይ በእስራኤል እና ሊባኖስ መካከል በአሜሪካ አደራዳሪነት የተኩስ አቁም ተደርሷል።

    የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር በቤካ ቫሊ በሚገኝ ማሽጋሃራ በተሰኘ መንደር በተፈጸመ ጥቃት ሁለት ሕጻናትን ጨምሮ 11 ሰዎች መገደላቸውን አስታውቋል።

    የእስራኤል ጦር ግን “የአሸባሪዎች እንቅስቃሴ” በታየበት አካባቢ ጥቃት መፈጸሙን ተናግሯል።

    የእስራኤል ጦር ጥቃቱን አጠናክሮ የቀጠለው ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በሄዝቦላህ ዒላማዎች ላይ “ጠንከር ያለ ጥቃት” እንዲፈጸም ትዕዛዝ ከሰጡ በኋላ ነው።

    በሁለቱ አገራት መካከል የተደረሰው የተኩስ አቁም በተደጋጋሚ ተጥሷል።

    እስራኤል በተለይ በደቡባዊ ሊባኖስ በተደጋጋሚ የአየር ድብደባ የምትፈጽም ሲሆን ሄዝቦላህም ሮኬቶችን እና ድሮኖችን በሰሜን እስራኤል ወደሚገኙ አካባቢዎች ይተኩሳል።

  3. ኢራን፣ አሜሪካ የፈጸመችው አዲስ ጥቃት የተኩስ አቁሙን የጣሰ ነው አለች

    አሜሪካ ራስን መከላከል በሚል አዲስ ጥቃት በደቡባዊ ኢራን ከፈጸመች በኋላ ቴህራን ዋሺንግተን የተኩስ አቁሙን ጥሳለች ስትል ከሰሰች።

    የአሜሪካው ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ በበኩላቸው በሁለቱ አገራት መካከል የሚደረገውን ጦርነት ለማስቆም የሚደረገው ድርድር “ጥቂት ቀናት ሊወስድ ይችላል” ብለዋል።

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አሜሪካ በደቡባዊ ኢራን ሆርሞዝጋን አውራጃ ጥቃት መፈጸሟን አስታውቆ የተኩስ አቁሙ “ግልጽ ጥሰት ነው” ሲል ተናግሯል።

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመግለጫው አሜሪካ “ጠብ አጫሪ እና ተቀባይነት ለሌለው ድርጊቷ” ተጠያቂ ትሆናለች ብሏል።

    አሜሪካ ጥቃት የፈጸመችበት ሆርሞዝጋን ክልል ከሆርሙዝ ወሽመጥ ጋር የሚዋሰን ነው።

    ኢራን በመግለጫው “ያለምንም ጥርጥር የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ምላሽ ሳይሰጥ የሚተወው ምንም ክፋት የለም እንዲሁም የኢራን ዜጎችን ከመከላከልም ወደ ኋላ አይልም” ብላለች።

    ሁለቱ አገራት እስከ ትናንት ሰኞ ድረስ በመግባቢያ ሰነዱ ዙሪያ የሚደረገው ንግግር ለውጥ ማሳየቱን ሲናገሩ ነበር።

    አሜሪካ እና ኢራን የሚያደርጉት ንግግር በስምምነት ከተቋጨ ለሦስት ወር የዘለቀውን ጦርነቱን ያስቆማል፣ የሆርሙዝ ወሽመጥን ያስከፍታል እንዲሁም የተኩስ አቁሙን በ60 ቀናት ይራዘማል ተብሎ ነበር።

    የአሜሪካ ጦር በደቡብ ኢራን የሚገኙ የሚሳዔል ማከማቻዎች እና ፈንጂ የሚጥሉ ጀልባዎችን ዒላማ በማድረግ አዲስ ዙር ጥቃት መክፈቱን አስታወቋል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ባወጣው መግለጫ ጥቃቱ “ራስን መከላከል” እንደሆነ አስታውቋል። ዓላማውም “በኢራን ኃይሎች ስጋት የተጋረጠባቸው ወታደሮቻችንን መከላከል ነው” ብሏል።

  4. የኢራኑ ጠቅላይ መሪ “ባሕረ ሰላጤው ከዚህ በኋላ የአሜሪካ ጦር ሰፈር መጠለያ አይሆንም” አሉ

    የኢራኑ ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ ለኢድ አል አድሃ በዓል ባስተላለፉት መልዕክት እስራኤልን “አደገኛ” በማለት ከዚህ በኋላ የፋርስ ባሕረ ሰላጤ አካባቢ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች መቀመጫ አይሆንም ሲሉ ገለጹ።

    ጠቅላይ መሪው በጽሁፍ ባስተላለፉት እና በመንግሥት ቴሌቪዥን በተነበበው መልዕክታቸው ላይ እስራኤልን “በቀጣናው አደገኛ እና ገዳይ ህመም” በማለት “መወገድ ይገባታል” ማላታቸውን ኢራኑ ዜና ወኪል ታስኒም ዘግቧል።

    ሞጅታባ የአባታቸው መገደል ተከትሎ የጠቅላይ መሪነቱን ሥልጣን ከተረከቡ በኋላ እስካሁን ድረስ ለሕዝብ በይፋ ያልታዩ ሲሆን፣ መልዕክታቸውን በጽሁፍ ሲያስተላልፉ ቆይተዋል።

    በአሁኑ መልዕክታቸው በኢራን ላይ ጦርነት ከተከፈተ በኋላ ነገሮች እየተቀያየሩ መሆናቸውን በማንሳት የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች በባሕረ ሰላጤው አገራት ውስጥ ቦታ እንደማይኖራቸውን ገልጸዋል።

    ጠቅላይ መሪው "ጊዜን ወደ ኋላ መመለስ እንደማይቻል እርግጥ እንደሆነው ሁሉ፤ በቀጣናው ያሉ አገራት እና መሬት ከዚህ በኋላ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች መጠለያ አይሆኑም” ሲሉ የአሜሪካ ሚና በአካባቢው እንደማይኖር አመለክተዋል።

    ጨምረውም "በቀጣናው ለክፉ ተግባር መጠለያ የሆኑት ጦር ሰፈሮች አይኖሩም እንዲሁም ተጨማሪ ወታደራዊ ሰፈሮች አይመሠረቱም” በማለት “አሜሪካ ከቀን ወደ ቀን ከዚህ በፊት ከነበረችበት ደረጃ እየወረደች ነው” ብለዋል።

    ጠቅላይ መሪው ባለፉት ወራት በተካሄደው ጦርነት አሜሪካ እና እስራኤል ከባድ ጉዳት እንደደረሰባቸው በመጥቀስ “በኢራን ከባድ ምት እስራኤል አቅመ ቢስ” እንደሆነች እና አሜሪካም “ከባድ ጥፊ እንደቀመሰች” ገልጸዋል።

  5. ኢራን “የአጸፋ እርምጃ መውሰድ ተገቢ እና የማይቀር” መሆኑን ገለጸች

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ፤ በአሜሪካ ጦር ለሚፈጸም ማንኛውም የተኩስ አቁም ጥሰት “የአጸፋ እርምጃ መውሰድ ተገቢ እና የማይቀር” እንደሆነ አስታወቀ።

    እስላማዊ አብዮታዊ ዘቡ አሜሪካ በደቡብ ኢራን የከፈተችውን ጥቃት ሳይጠቅስ በሕዝብ ግንኙነቱ በኩል ባወጣው መግለጫ “የአሜሪካ ጦር በቀጣናው ጣልቃ ገብነቱን እና ጠብ ጫሪነቱን ቀጥሎ በፐርዥያ ባሕረ ሰላጤ ወደ ኢራን የአየር ክልል እና ወደ እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ መከላከያ ሰፈር ገብቷል” ብሏል።

    “በጥንቃቄ የደኅንነት ቅኝት ካደረግን በኋላ የግዛት ሉዓላዊነታችንን ለመከላከል ኤምኪው-9 ድሮን መትተን ጥለናል” ሲልም አክሏል።

    አርኪው-4 ድሮን እና ኤፍ-35 ተዋጊ ጄት እንደመታ እና እርምጃው “በውሃ የተሸፈነውን አካባቢ ጥለው እንዲሸሹ እንዳስገደዳቸው” አስታውቋል።

    እነዚህ ጥቃቶች መቼ እና የት እንደተፈጸሙ በግልጽ አላስቀመጠም።

    የአሜሪካ ጦር ባወጣው መግለጫ በደቡብ ኢራን የሚገኙ የሚሳዔል ማከማቻዎች እና ፈንጂ የሚጥሉ ጀልባዎችን ዒላማ በማድረግ አዲስ ዙር ጥቃት መክፈቱን ይፋ አድርጓል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ጥቃቱ “ራስን መከላከል” እንደሆነ ገልጾ፤ ዓላማውም “በኢራን ኃይሎች ስጋት የተጋረጠባቸው ወታደሮቻችንን መከላከል ነው” ብሏል።

    የኢራን መገናኛ ብዙኃን ትናንት ምሽት በባንደር አባስ የወደብ ከተማ አውሮፕላን ማረፊያ አቅራቢያ ፍንዳታ መሰማቱን ዘግበዋል።

  6. ኳታር ለኢራን 12 ቢሊየን ዶላር ልትሰጥ ነው መባሉን አስተባበለች

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር በሚደረገው ድርድር ከስምምነት እንድትደርስ ለማድረግ 12 ቢሊዮን ዶላር ለመስጠት ሃሳብ አቅርባለች መባሉን መሠረተ ቢስ በማለት ኳታር አስተባበለች።

    የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማጂድ አል እንሳሪ በኤክስ የሶሻል ሚዲያ መድረክ ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ የአገራቸው ዲፕሎማሲያዊ ሚና በግልጽ የሚታወቅ መሆኑን በመጥቀስ የወጡ ዘገባዎች ያላትን “ታማኝ ዓለም አቀፍ የሰላም ጥረቶች አመቻችንት የሚያጠለሽ ነው” ብለዋል።

    ይህ የሚኒስትሩ አስተያየት የተሰማው በርካታ ከፍተኛ የኢራን ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ጋር የሚደረገውን ድርድር ለመቋጨት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ኳታርን እየጎበኙ ባለበት ጊዜ ነው።

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር በሚደረገው ድርድር በኳታር ያለውን ጨምሮ በውጭ አገራት እንዳይንቀሳቀስ የታገደባት ሃብቷ እንዲለቀቅ እየጠየቀች ነው። ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት አገሪቱ በኳታር ውስጥ 12 ቢሊዮን ዶላር የሚሆን ገንዘብ ታግዶባታል።

    በኒውክሌር መረሃ ግብሯ ምክንያት ከምዕራበባውያን በተለይም ከአሜሪካ ጋር በገባችው እሰጣ ገባ ተደራራቢ ዕቀባ የተጣለባት ኢራን ባለፈው የካቲት ወር በአሜሪካ እና በእስራኤል በተከፈተባት ጥቃት ጦርነት ውስጥ ገብታለች።

    ለጥቂት ወራት የዘለቀው ጦርነት በተኩስ አቁም ጋብ ብሎ በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ድርድር እየተደረገ የሚገኝ ሲሆን፣ ኢራን ከስምምነት ለመድረስ በቅድመ ሁኔታ ካቀረበቻቸው ነጥቦች መካከል በውጭ ያለው ሃብቷ እንዲለቀቅላት የሚጠይቀው ይገኝበታል።

  7. በኢራን ጦርነት ምክንያት በመላው ዓለም የሚሳዔል መከላከያ ሥርዓት መዳከሙን ዘለንስኪ ተናገሩ

    የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዘለንስኪ “በኢራን ጦርነት ምክንያት በመላው ዓለም የባለስቲክ ሚሳዔል መቃወሚያ ሥርዓት እጥረት ተፈጥሯል” አሉ።

    ለተፈጠረው እጥረት “መፍትሔ መገኘት አለበት” ሲሉም ፕሬዝዳንቱ አሳስበዋል።

    ዘለንስኪ አክለውም “የዩክሬንን የአየር መከላከያ ለማጠናከር ከሁሉም አካላት ጋር እየሠራን እንገኛለን። ቅድሚያ የምንሰጠው ጉዳይ ነው” ብለዋል።

    በዩክሬን መዲና ኪቭ “ስልታዊ ጥቃቶች” እንደምትሰነዝር ያስታወቀችው ሩሲያ በበኩሏ የውጭ አገራት ዜጎች ከተማዋን ለቅቀው እንዲወጡ ማሳሰቢያ ሰጥታለች።

    የዩክሬኑ ፕሬዝዳንት ዘለንስኪ፤ አሜሪካ ለአገራቸው ተጨማሪ ድጋፍ የምታደርግበትን መንገድ በተመለከተ ውይይቶች ይቀጥላሉ ብለዋል።

    አውሮፓ በቂ የሚሳዔል መቃወሚያ ሥርዓት እንዲኖራት በሚል ዩክሬን መሣሪያውን የምታመርትበትን ፍጥነት መጨመሯንም ገልጸዋል።

  8. ማርኮ ሩቢዮ ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ የመድረስ ዕድል መኖሩን በድጋሚ ገለጹ

    ዋሽንግተን ቴህራን ላይ አዲስ ጥቃት ብትከፍትም ስምምነት ላይ መድረስ የሚቻልበት ዕድል “አሁንም እንዳለ” የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስር ማርኮ ሩቢዮ ተናገሩ።

    አሜሪካ ያደረሰችው ጥቃት የኢራን የሚሳዔል ሥርዓት እና ጀልባዎች ላይ ጉዳት ቢያደርስም ሩቢዮ ዛሬ ባደረጉት ንግግር የስምምነት ላይ መድረስ ይቻላል ብለዋል።

    “በኳታር በሚደረገው ውይይት ለውጥ የሚመጣ ከሆነ እናያለን” ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ “ፕሬዝዳንቱ ግሩም ስምምነት ላይ ይደርሳሉ፤ አልያም ስምምነት አይኖርም” ሲሉ ገልጸዋል።

    በኳታር በሚደረገው ውይይት ላይ የቀረበው የሰላም ዕቅድ ውስጥ ያለው “የቃላት አጠቃቀም እና ምርጫ መታየት ስላለት” ንግግሩ ቀናት ሊወስድ እንደሚችል ጠቁመዋል።

    የሆርሙዝ ወሽመጥ መከፈት እንዳለበት አስረግጠው የተናገሩት ማርኮ ሩቢዮ “እየሆነ ያለው ነገር ሕገ ወጥ ነው። ዓለም ላይ አለመረጋጋት ፈጥሯል፤ ተቀባይነትም የለውም” ሲሉ አክለዋል።

  9. በኪቭ “ስልታዊ ጥቃት” ለመሰንዘር የዛተችው ሩሲያ የውጭ ዜጎች ከከተማዋ እንዲወጡ አሳሰበች

    በዩክሬን መዲና ኪቭ አዲስ “ስልታዊ ጥቃቶች” እንደምትሰነዝር ያስታወቀችው ሩሲያ፤ የውጭ አገራት ዜጎች ከተማዋን ለቅቀው እንዲወጡ ማሳሰቢያ ሰጠች።

    ሩሲያ ከቀናት በፊት በዩክሬን መዲና ከፍተኛ ጥቃት ያደረሰች ሲሆን፤ ጦርነቱ ከተጀመረ ወዲህ የከፋው ነው ተብሏል።

    ሩሲያ በቀጣይ የምትፈጽመው ጥቃት “ውሳኔ የሚሰጥባቸው ማዕከላት ላይ ያነጣጠረ” መሆኑን አስታውቃለች።

    የሰው አልባ አውሮፕላን ማምረቻ ፋብሪካዎችን ጨምሮ ሌሎችም ተቋማት ዒላማ እንደሚደረጉ የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።

    የውጭ አገራት ዜጎች እና ዲፕሎማቶች ኪቭን “በተቻለው ፍጥነት” ለቅቀው እንዲወጡም መሥሪያ ቤቱ አሳስቧል።

    ዩክሬናውያን ከአስተዳደራዊ እና ወታደራዊ ተቋማት ሕንጻዎች እንዲርቁም አስጠንቅቋል።

    ዩክሬን በበኩሏ የሩሲያ ዛቻ “ሃፍረተ ቢስ የሆነ ጫና ማሳደሪያ መንገዷ ነው” ስትል አጣጥላለች።

    የዩክሬን አጋር አገራት ሞስኮ ላይ የሚያሳድሩትን ተጽዕኖ እንዲጨምሩም ጠይቃለች።

    ሩሲያ ለውጭ አገራት ዜጎች ማስጠንቀቂያ መስጠቷ “የውጭ ዲፕሎማቶች መቀመጫዎች ከዒላማዎቿ መካከል እንደሚገኙበት ያሳያል” ስትልም ዩክሬን ስጋቷን ገልጻለች።

  10. እስራኤል ሄዝቦላህ ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት እንደምታጠናክር ኔታንያሁ ተናገሩ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ሄዝቦላህ ላይ የሚፈጸመው ጥቃት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል መናገራቸውን ተከትሎ የአገሪቱ ጦር በመላው ሊባኖስ አዲስ ዙር ጥቃት ማድረስ መጀመሩን አስታወቀ።

    የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት በምስራቅ ሊባኖስ በሚገኘው ቤካ ሸለቆ እና በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ላይ ጥቃት በመክፈት ሄዝቦላህን እየመታ መሆኑን ገልጿል።

    ሄዝቦላህ በበኩሉ የእስራኤል ወታደሮች፣ ታንኮች፣ የጦር ሰፈሮች፣ ሕንፃዎች እና ሌሎች ስፍራዎችን ዒላማ ያደረጉ 22 የድሮን እና የሮኬት ጥቃቶችን በመፈጸም አጸፋውን መመለሱን አስታውቋል።

    ሊባኖስ እና እስራኤል በዚህ ወር መጀመሪያ የደረሱበትን ተኩስ አቁም በ45 ቀናት ለማራዘም ስምምነት ቢፈጽሙም ውጊያው ቀጥሏል።

    ኔታንያሁ ሰኞ ምሽት በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት፤ እስራኤል “ከሄዝቦላህ ጋር ጦርነት ላይ” እንደሆነች ተናግረዋል። ሠራዊቱ “አድቃቂ ምት” እንዲፈጽም ማዘዛቸውንም ገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ እስራኤል በከፈተችው ወታደራዊ ዘመቻ "ከ600 በላይ አሸባሪዎች” መገደላቸውንም ተናግረዋል። "አሁን ከእኛ የሚጠበቀው ጥቃቱን ማጠናከር እና ጥንካሬውን ይበልጥ መጨመር ነው" ሲሉም ተደምጠዋል።

    ቤዛልል ስሞትሪች እና ኢታማር ቤን ግቪር የተባሉት ሁለት ቀኝ አክራሪ የእስራኤል ሚኒስትሮች ሊባኖስ ውስጥ የሚካሄደውን ጨምሮ የጦሩ ወታደራዊ ዘመቻ እንዲስፋፋ ጠይቀዋል።

    ሰኞ ዕለት ድሮኖች እና ሮኬቶችን በመጠቀም በደቡብ ሊባኖስ እንዲሁም በሰሜን እስራኤል የሚገኙ ስፍራዎችን ማጥቃቱን የገለጸው ሄዝቦላህ፤ እርምጃውን የወሰደው በእስራኤል “የተኩስ አቁም ጥሰት” ምክንያት እንደሆነ ተናግሯል።

    ይፋዊ የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የሌላቸው ሊባኖስ እና እስራኤል በሚቀጥለው ሳምንት ዋሽንግተን ውስጥ ተጨማሪ ድርድር ለማድረግ ቀጠሮ ይዘዋል። የሊባኖስ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ አውን፤ የእስራኤል ጦር ከደቡብ ሊባኖስ ሙሉ በሙሉ እንዲወጣ ጠይቀዋል።

  11. የአሜሪካ ጦር በደቡብ ኢራን አዲስ ጥቃት መክፈቱን አስታወቀ

    የአሜሪካ ጦር በደቡብ ኢራን የሚገኙ የሚሳዔል ማከማቻዎች እና ፈንጂ የሚጥሉ ጀልባዎችን ዒላማ በማድረግ አዲስ ዙር ጥቃት መክፈቱን አስታወቀ።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ባወጣው መግለጫ ጥቃቱ “ራስን መከላከል” እንደሆነ አስታውቋል። ዓላማውም “በኢራን ኃይሎች ስጋት የተጋረጠባቸው ወታደሮቻችንን መከላከል ነው” ብሏል።

    የማዕከላዊ ዕዙ ቃል አቀባይ ካፕቴን ቲም ሀውኪንስ “የአሜሪካ ጦር በተኩስ አቁሙ መሠረት ቢታቀብም ወታደሮችን ይከላከላል” ብለዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጊ ከአሜሪካ ጋር የሚደረገው ድርድር መሻሻል ቢያሳይም ግጭቱን የሚያስቆም ስምምነት ላይ “በቅርብ ጊዜ እንደማይደረስ” መግለጻቸው ይታወሳል።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ቃል አቀባይ እንደተናገሩት እንደ አዲስ የተከፈተው ጥቃት የተፈጸመው በደቡባዊ የኢራን ግዛት የምትገኘው ባንዳር አባስ የወደብ ከተማ ላይ ነው።

    የወደብ ከተማዋ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚገኘው የኢራን ባሕር ኃይል መቀመጫ መሆኗን የኒው ዮርክ ታይምስ ዘገባ ይጠቁማል።

    የኢራን ብሔራዊ ጣቢያ እንደዘገበው የከተማዋ ባለሥልጣናት ፍንዳታ መስማታቸውን ተከትሎ ምርመራ ማካሄድ ጀምረዋል።

    ኢራን ከአሜሪካ ለተከፈተባት ጥቃት እስካሁን ምላሽ አልሰጠችም። የአሁኑ ጥቃት በሁለቱ አገራት የሰላም ድርድር ላይ ምን ጫና እንደሚያሳድርም ግልጽ አይደለም።

    ጥቃቱን ተከትሎ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ “አሁንም ቢሆን ስምምነት ላይ መድረስ ይቻላል” ብለዋል።

    ትናንት የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ከኳታር ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር ውይይት አድርገዋል።

  12. ትራምፕ አረብ እና ሙስሊም አገራት ከእስራኤል ጋር ስምምነት እንዲፈርሙ ግፊት እያደረጉ ነው

    አሜሪካ ከኢራን ጋር ከስምምነት ለመድረስ መቃረቧን እየገለጹ ያሉት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከዚያ በፊት ግን ዋነኞቹ ሙስሊም አገራት ከእስራኤል ጋር የአብረሃም ስምምነትን እንዲፈርሙ ጥሪ አቀረቡ።

    ድርድሩ “በጥሩ ሁኔታ እየተካሄደ ነው” ያሉት ፕሬዝዳንቱ ከኢራን ጋር የሚካሄደውን ጦርነት የሚያስቆመው ስምምነት ከመፈረሙ በፊት ብዙሃኑ ሕዝባቸው ሙስሊም የሆኑ ስድስት አገራት ከእስራኤል ጋር ያላቸውን ግንኙነት የሚያሻሽለውን ስምምነት መፈረም እንዳለባቸው አስታውቀዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚደረገውን ስምምነት ከስድስት ዓመት በፊት ዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ እና ባህሬን በማስከተልም ሞሮኮ እና ሱዳን ከእስራኤል ጋር ከተፈራረሙት የአብረሃም ስምምት ጋር አስተሳስረው እያቀረቡት ነው።

    ከበርካታ ሙስሊም እና አረብ አገራት መሪዎች ጋር መነጋገራቸውን በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የጠቀሱት ትራምፕ ውስብስቡን ሥራ አሜሪካ መሥራቷን በመግለጽ “በተከታይነት እነዚህ አገራት በሙሉ ቢያንስ የአብረሃም ስምምነትን መፈረም ይጠበቅባቸዋል” ብለዋል።

    ከእነዚህም መካከል ሳዑዲ አረቢያ፣ ኳታር፣ ፓኪስታን፣ ቱርክ፣ ግብፅ እና ዮርዳኖስን በመጥቀስ ስምምነቱን እንዲፈርሙ እንደሚፈልጉ አስታውቀዋል።

    ነገር ግን ግብፅ እና ዮርዳኖስ ከእስራኤል ጋር ግንኙነት ያላቸው ሆነው ሳለ ለምን እንደጠቀሷቸው ግልጽ አይደለም። እስራኤል ከቱርክ ጋር ለረጅም ጊዜ የቆየ የሻከረ ግንኙነት ያላት ሲሆን፣ የጋዛውን ጦርነት ተከትሎ የበለጠ ተቃቅረዋል።

    የተጠቀሱት አገራት የአብረሃም ስምምነትን የሚፈርሙ ከሆነ እስራኤል ከአብዛኞቹ አረብ እና ሙስሊም አገራት ጋር ያላትን ግንኙነት በከፍተኛ ሁኔታ የሚያሻሽል ነው።

  13. አንድ መኪና ከዝሆን ጋር ተጋጭቶ ሦስት ሰዎች ሲሞቱ አራት ቆሰሉ

    በኡጋንዳ ብሔራዊ ፓርክ ውስጥ አንድ መኪና ከዝሆን ጋር ተጋጭቶ ቢያንስ ሦስት ሰዎች መሞታቸውን ባለሥልጣናት አስታወቁ።

    ፖሊስ እንዳለው እሁድ ማታ በኡጋንዳ ሰሜናዊ ምዕራብ ክፍል ውስጥ በተከሰተው አደጋ ከሞቱት በተጨማሪ ሌሎች አራት ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    ተሽከርካሪው ሰባት የአገሪቱ ገቢዎች ባለሥልጣናትን አሳፍሮ እየተጓዘ ሳለ ነበር ከዝሆኑ ጋር የተጋጨው። በአደጋው የተጎዱት ሰዎች በአካባቢው ወደሚገኝ ከዚያም ወደ ዋና ከተማዋ ካምፓላ ተወስደዋል።

    ስለአደጋው መግለጫ ያወጡት ባለሥልጣናት በሰዎች ላይ የሞት እና የአካል ጉዳት ከመድረሱ ውጪ በዝሆኑ ላይ ስለደረሰው ጉዳት ያሉት ነገር የለም።

    በኡጋንዳ ውስጥ ከዱር እንስሳት ጋር በተያያዘ የሚከሰት የመኪና አደጋ በተደጋጋሚ እንደሚያጋጥም ይነገራል። የአገሪቱ የዱር እንስሳት ባለሥልጣን አሽከርካሪዎች በመንገዳቸው ላይ ለእንስሳት ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል።

    "አሽከርካሪዎች ለእንስሳት በተከለሉ ጥብቅ አካባቢዎች በኩል በሚያልፉበት ጊዜ እንስሳቱ በብዛት መንገዶችን ስለሚያቋርጡ በጥንቃቄ እንዲያሽከረክሩ” ጠይቋል።

  14. ትራምፕ ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ ሊደረስ እንደሚችል ተናገሩ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር ስምምነት ላይ ሊደረስ የሚችልበት እንዳለ አስረግጠው ተናገሩ።

    ከቴህራን ጋር እየተካሄደ ያለውን ድርድር አጥብቀው የተከላከሉት ፕሬዝዳንቱ የተቿቸውን ዴሞክራቶች እና ሪፐብሊካኖች “ከኢራን ጋር የሚካሄደው ድርድር ስላለው አቅም የማያውቁ ደደቦች” ሲሉም አንቋሸዋል።

    በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ ፖለቲከኞቹን “ትልልቅ ድሎቼን የሚኮንኑ ከፋፋይ ግለሰቦች” ብለዋል።

    “ከኢራን ጋር የሚደረሰው ስምምነት ታላቅ እና ትርጉም ይሆናል፤ አልያም ምንም ስምምነት አይኖርም” ሲሉም ትራምፕ ተናግረዋል።

    የትራምፕ አስተዳደር በኢራን ያለው ፖለቲካዊ ዓላማ ላይ ዴሞክራቶች እና ሪፐብሊካን የሕዝብ እንደራሴ አባላትም ሳይቀር ጥያቄ ማንሳት ጀምረዋል።

    ከቴህራን ጋር የሚደረገውን ንግግር ከተቹ መካከል የቀድሞው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማይክ ፖምፔዮ እና የቀድሞ የትራምፕ የብሔራዊ ደኅንነት አማካካሪ ጆን ቦልተን ይጠቀሳሉ።

  15. ከፍተኛ የኢራን ባለሥልጣናት ኳታር መግባታቸው ተዘገበ

    ከአሜሪካ ጋር የሚደረገውን የሰላም ድርድር በዋነኛነት የሚመሩት የኢራን ባለሥልጣናት ኳታር ዋና ከተማ ዶሃ መግባታቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘገበ።

    የኢራን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ መሐመድ ባጋር ጋሊባፍ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አባስ አራግቺ ወደ ኳታር ያደረጉት ጉዞ የተጠበቀ እንዳልሆነ ተገልጿል።

    የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ከሼኽ ታሚም ቢን ሐማድ አል ታሒኒ ጋር ውይይት ለማድረግ ዶሃ መሄዳቸው ተዘግቧል።

    ውይይታቸው በዋነኛነት የሆርሙዝ ወሽመጥ እና የዩራንየም ጉዳይን የሚመለከት እንደሚሆን የሮይተርስ ዘገባ ያመለክታል።

    የኢራን ብሔራዊ ባንክ ገዢ አብዶልናስር ሔማቲ “ማዕቀብ የተጣለባቸው የባንክ ሒሳቦችን በተመለከተ ለሚደረግ ድርድር” ወደ ኳታር ማቅናታቸውን የቴህራን መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ባለፈው ሳምንት ደግሞ የኳታር ልዑካን ወደ ኢራን አቅንተው እንደነበር ይታወሳል።

    ኢራን እንደ ቅድመ ሁኔታ ካቀረበቻቸው ነጥቦች መካከል አሜሪካ ከፋይናንስ ይዞታዎቿ ላይ ማዕቀብ እንድታነሳ የሚጠይቀው ይገኝበታል።

  16. ኢራን ከአሜሪካ ጋር በበርካታ ጉዳዮች ላይ መግባባቷን ነገር ግን ስምምነት ገና መሆኑን ገለጸች

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ሰኞ ዕለት ከአሜሪካ ጋር በቀረበው መግባቢያ ሰነድ በርካታ ጉዳዮች ከድምዳሜ ላይ መድረሳቸውን ገለጸች።

    ቃል አቀባዩ አክለውም ይህ ግን ቴህራን ስምምነት ለመፈረም ተቃርባለች ማለት አለመሆኑን አስታውቀዋል።

    ኢስማኤል ባጌይ ኢራን እየተነጋገረች ያለችው ጦርነቱን ለማቆም እንጂ በኒውክሌር ፕሮግራሟ ላይ አለመሆኑን ገልጸዋል።

    ቃል አቀባዩ የአሜሪካ ባለሥልጣናት የአቋም መለዋወጥ ለስምምነቱ እንቅፋት መሆኑን በማንሳት ከስሰዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ እሁድ ዕለት አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችው ዕገዳ “ከስምምነት ላይ እስክንደርስ፣ ስምምነቱ እስኪጸድቅ እና እስኪፈረም ድረስ በሙሉ ኃይል ተግባራዊነቱ ይቀጥላል” ብለዋል።

    አክለውም “ሁለቱም አካላት ጊዜ መውሰድ እና የሚገባ ነገር ላይ መድረስ አለባቸው” ሲሉ ጽፈዋል።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አክለውም ተወካዮቻቸው ከኢራን ጋር ስምምነት ለማድረግ እንዳይጣደፉ አሳስበዋል።

  17. ሩቢዮ የኢራን ጦርነትን ለማስቆም የሚያስችል ስምምነት “ምናልባት ዛሬ ሊደረስ” ይችላል አሉ

    የአሜሪካው ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ በሁለቱ አገራት መካከል ዛሬ ስምምነት ሊደርስ ይችላል አሉ።

    በሕንድ ዋና ከተማ ኒው ዴልሂ የሚገኙት ሩቢዮ በአሜሪካ እና ኢራን ተደራዳሪዎች “ጠረጴዛ ላይ ጠንካራ የስምምነት ነጥቦች” መኖራቸውን ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    ሩቢዮ አክለውም “ገና በሂደት ላይ ያለ ነገር ነው፤ ትናንት ማታ የሆነ ዜና ይኖረናል ብለን አስበን ነበር፥ ምናልባት ዛሬ ይኖረናል” ብለዋል።

    የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ ሰኞ ዕለት አገራቸው ከኢራን ጋር ጥሩ ስምምነት ታደርጋለች ወይም “በሌላ መንገድ” ትፈታዋለች ብለዋል።

    ሩቢዮ ሌሎች “አማራጮችን” ከመፈለግ በፊት ለዲፕሎማሲ ያለውን ዕድል ሁሉ መስጠት አስፈላጊ መሆኑን ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እሁድ ዕለት ተወካዮቻቸው ከኢራን ጋር ስምምነት ለማድረግ እንዳይጣደፉ አሳስበዋል።

    ሩቢዮ “ሆርሙዝን ለመክፈት የሚያስችል ተጨባጭ የሆነ ስምምነት ጠረጴዛው ላይ አለ። ወሽመጡን ክፈቱ፤ ተጨባጭ፣ እውነተኛ በጊዜ የተገደበ ድርድር ወደ ማድረግ ግቡ፤ እናም ተስፋ አለኝ እናሳካዋለን” ብለዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አክለውም “በፍጥነት ከድምዳሜ ላይ መድረስ አልፈልግም” በማለት “ከኢራን ምላሽ ለማግኘት ትንሽ ጊዜ ይወስዳል” ሲሉም ተደምጠዋል።

    እሁድ ዕለት ፕሬዚዳንት ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ላይ አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችው ዕገዳ “ከስምምነት ላይ እስክንደርስ፣ ስምምነቱ እስኪጸድቅ እና እስኪፈረም ድረስ በሙሉ ኃይል ተግባራዊነቱ ይቀጥላል” ብለዋል።

    አክለውም “ሁለቱም አካላት ጊዜ መውሰድ እና የሚገባ ነገር ላይ መድረስ አለባቸው” ሲሉ ጽፈዋል።

    የኢራን መንግሥት በትራምፕ ሆነ በሩቢዮ አስተያየቶች ላይ አስተያየቱን አልሰጠም።

    ታስኒም የዜና ወኪል ግን አሜሪካ የስምምነቱ ወሳኝ ነጥቦችን እያስተጓጎለች ነው በማለት እንዳይንቀሳቀሱ የታገዱ ፈንዶች እንዲለቀቁ ጠይቋል።

    የኢራን ፓርላማ ቃል አቀባይ ኢብራሂም ሬዛይ በበኩላቸው በጦርነቱ ወቅት “ዓይን ላጠፋ ዓይን” የሚል መርህ ሲከተሉ እንደነበር ገልጸው፤ በዲፕሎማሲ አለመግባባት ወቅት ደግሞ “ለተግባር ተግባራዊ ምላሽ መስጠት” የሚል መሆኑን ተናግረዋል።

    በኤክስ ገጻቸው ላይ ኢራን በጫናዎች ወይንም ማስፈራሪያዎች አትንበረከክም ያሉት ቃል አቀባዩ፤ አሜሪካ ስምምነት ላይ መድረስ የምትፈልግ ከሆነ መደራደር አለባት ነገር ግን ነዳጅ በ6 ዶላር ማግኘት የምትፈልግ ከሆነ ማስመሰሏን ትቀጥል ሲሉ ጽፈዋል።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሰላም ስምምነት ይፈረማል የሚል ተስፋ እየጨመረ በመምጣቱ ሰኞ ዕለት የዓለም የነዳጅ ዋጋ በ6 በመቶ ገደማ ቀንሷል።

  18. የዩኬ መከላከያ ሚኒስቴርን ጭኖ የነበረ ጄት በሩሲያ ድንበር አቅራቢያ ሲግናሉ ተጠለፈ

    የዩናይትድ ኪንግደም ሮያል አየር ኃይል ጄት ባለፈው ሳምንት የአገሪቱን መከላከያ ሚኒስትርን ጭኖ በሩሲያ ድንበር አቅራቢያ በሚበርበት ሰዓት ሲግናሉ ተጠልፎ (Jamming) እንደነበር ተገልጸ።

    ክስተቱ ያጋጠመው መከላከያ ሚኒስትሩ ጆን ሃሌይ ኢስቶኒያ ውስጥ የሚገኙ የብሪታኒያ ወታደሮችን ጎብኝተው ሲመለሱ እንደነበር የዩኬው ታይምስ ጋዜጣ ዘግቧል።

    ጥቃቱ የአውሮፕላኑ አቅጣጫ ጠቋሚ ‘ጂፒኤስ’ እንዲያጠፋ የሚያደርግ በመሆኑ አብራሪዎቹ ሌላ የጉዞ ስርዓት ለመጠቀም ተገድደዋል። ሦስት ሰዓት በሚፈጀው በረራ ላይ ከተፈጸመው ጥቃት ጀርባ ሩሲያ እጇ እንዳለ ተገምቷል።

    ይህ ጠለፋ ያጋጠመው፤ ሁለት የሩሲያ የጦር አውሮፕላኖች ባለፈው ወር በጥቁር ባሕር በኩል ሲበር የነበረ የዩናይትድ ኪንግደም የስለላ አውሮፕላንን “በተደጋጋሚ እና በአደገኛ ሁኔታ” መጥለፋቸው ይፋ በተደረገ ማግሥት ነው።

    የአሁኑ ጥቃት የተፈጸመው የመከላከያ ሚኒስትሩን ዒላማ በማድረግ መሆኑ አልተረጋገጠም። ነገር ግን የአውሮፕላኑ ጉዞ በበረራ መከታተያ ድረ ገጾች ላይ ወጥቶ እንደነበር ጋዜጣው ዘግቧል።

    ቢቢሲ ስለ ጉዳዩ የመከላከያ ሚኒስቴርን አስተያየት ጠይቋል።

    መከላከያ ሚኒስትሩ በኢስቶኒያ ቆይታቸው በሩሲያ ድንበር አቅራቢያ በሚካሄድ የኔቶ ወታደራዊ ልምምድ ላይ የሚሳተፉ የዩኬ ሠራዊት አባላትን አነጋግረዋል።

    ባለፈው ወር ደግሞ የሩሲያ ሱ-35 ተዋጊ ጄት ‘ሩቬት ጆይንት’ የተባለውን የስለላ አውሮፕላንን እጅግ ተጠግቶ አውቶፓይለቱን እንዲጠፋ በማድረግ የአውሮፕላኑ አደጋ ጊዜ ስርዓቱ እንዲበራ አድርጎ ነበር።

    ሌላ ሱ-27 ጄት ደግሞ ስድስት ጊዜ በዩናይትድ ኪንግደም አውሮፕላን ፊት እንዳለፈ እና ስድስት ሜትር ርቀት ድረስ ወደ አውሮፕላኑ አፍንጫ እንደተጠጋ ተገልጿል።

  19. በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሰላም ስምምነት ይደረሳል በሚል ተስፋ የነዳጅ ዋጋ ቅናሽ አሳየ

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሰላም ስምምነት ይፈረማል የሚል ተስፋ በስፋት በመታየቱ የነዳጅ ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ቀነሰ። የእስያ የአክሲዮን ገበያዎች ላይም ጭማሪ ታይቷል።

    ቅዳሜ ዕለት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከቴህራን ጋር የሰላም ስምምነቱ ነጥቦች "በአብዛኛው ድርድር ተደርጎባቸዋል" በማለት ዝርዝሩን ይፋ ሳያደርጉ ቀርተዋል።

    ሁለቱ አገራት በበርካታ ጉዳዮች ላይ መስማማታቸው ሲገለጽ ቢቆይም ትራምፕ ተደራዳሪዎች ከኢራን ጋር ስምምነት ለመፈራረም እንዳይጣደፉ አሳስበዋል።

    ሰኞ ጠዋት በእስያ ገበያ ብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ 5.5 በመቶ ቅናሽ ያሳየ ሲሆን በአሜሪካ ደግሞ የ5.8 በመቶ ቀንሶ 90.99 ዶላር ተሸጧል።

    ትራምፕ ከኢራን ጋር የሚደረገው ድርድር የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም ማስከፈትን የሚያካትት ነው ያሉ ሲሆን ይህም ለወራት መንቀሳቀሻ አጥተው የቆሙ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን በነጻነት እንዲጓዙ ያስችላል ተብሎ ነበር።

    ጠባቡ የባሕር መተላለፊያ የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚተላለፍበት ሲሆን ከየካቲት 21 2018 ዓ.ም. በኋላ ተዘግቷል።

    ቅዳሜ ዕለት ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ከሳዑዲ አረቢያ፣ ከዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ፣ ኳታር ጋር “በሰላም ስምምነቱ የመግባቢያ ሰነድ” ዙሪያ “ጥሩ ውይይት” ማድረጋቸውን ገልጸዋል።

  20. ፕሬዝዳንት ትራምፕ የአሜሪካ ተደራዳሪዎች ከኢራን ጋር ስምምነት ለመፈጸም "እንዳይጣደፉ" አሳሰቡ

    አሜሪካ እና ኢራን ጦርነቱን ለመቋጨት የሚያደርጉት ድርድር ወደ ማጠናቀቂያው እንደተቃረበ መነገሩን ተከትሎ፤ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተደራዳሪዎቻቸው ከኢራን ጋር “ተጣድፈው ወደ ስምምነት እንዳይገቡ” አዘዙ።

    በሁለቱ አገራት ንግግር እየተደረገበት ያለው የስምምነት ዕቅድ ከያዛቸው ነጥቦች መከካከል የተኩስ አቁሙን ለ60 ቀናት ማራዘም፣ የሆርሙዝ ወሽመጥን በድጋሚ መክፈት እንዲሁም የኢራንን የኒውክሌር ፕሮግራም በተመለከተ ተጨማሪ ድርድር ማካሄድ የሚሉት ይገኙበታል።

    ትራምፕ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ ንግግሩ “ገንቢ” በሆነ ሁኔታ እየተካሄዱ መሆኑን ቢገልጹም፤ አክለው ግን “ሁለቱም ወገኖች ጊዜያቸውን መውሰድ እና በትክክል ማከናወን አለባቸው” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ቅዳሜ ዕለት ስምምነቱ “በአብዛኛው ድርድር እንደተደረገበት” መገናራቸው ስምምነት ይፋ መደረጉ አይቀሬ ነው የሚል ግምት ፈጥሮ ነበር።

    የኢራን ባለሥልጣናትም ተመሳሳይ ሀሳብ አመልክተው ነበር። የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ሁለቱ ወገኖች ስምምነት ላይ ለመድረስ “እጅግ ቅርብ እና እጅግ ሩቅ” ናቸው ብለው ነበር።

    የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡ ከሆነ ድርድር የሚካሄድበት እቅድ የመጨረሻው ስምምነት አይደለም። ይልቁንም ሁለቱ አገራት የተወሰኑ አጨቃጫቂ ጉዳዮች በኋላ ድርድር እንዲካሄድባቸው እንደሚፈቅድ ዘግበዋል።

    ኢራን ላይ የተጣለው ማዕቀብ የሚነሳበት መጠን እና ጊዜ፣ የታገደውን የኢራን ገንዘብን የማስለቀቅ ጉዳይ እንዲሁም አሜሪካ የቴህራንን የኒውክሌር ፍላጎት ለመገደብ ያላት ፍላጎት ለበኋላ ድርድር ከሚተዉ ነጥቦች መካከል ናቸው።

    ይህ የስምምነት ዕቅድ ሪፐብሊካኖችን ለሁለት የከፈለ ሲሆን የተወሰኑት ኢራን ላይ ለዘብተኛ አቋም የያዘ እንደሆነ በይፋ እየተናገሩ ነው።

    ትራምፕ እሁድ ዕለት በትሩዝ ሶሻል ገጻቸው ባጋሩት ልጥፍ፤ ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ ልትሰራ እንደማትችል “መረዳት እንዳለባት” በአጽንኦት አንስተዋል። ቴህራን የኒውክሌር ፕሮግራሟ ለሰላማዊ ዓላማ እንደሚውል በተደጋጋሚ ስትገልጽ ቆይታለች።

    አንዳንድ የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ከኢራን ጋር በሚደረሰው ስምምነት አማካኝነት ኢራን የበለጸገ ዩራኒየሟን አሳልፋ እንደምትሰጥ ዘግበዋል።

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ለአገሪቱ ቴሌቪዥን በሰጡት ቃለ መጠይቅ ቴህራን “ፍላጎቷ የኒውክሌር መሣሪያ እንዳልሆነ ለዓለም ለማረጋገጥ” ዝግጁ እንደሆነች ተናግረዋል።

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ በበኩላቸው በድርድሩ “ጉልህ” መሻሻል ቢታይም፤ ሂደቱ “የመጨረሻ ደረጃ እንዳልደረሰ” ገልጸው ነበር።