የአሜሪካዊው የቀይ ካርድ ቅጣት ተግባራዊ አለመሆን ከባድ ተቃውሞ ቀሰቀሰ
ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከፊፋ ፕሬዝዳንት ጋር በስልክ ከተነጋገሩ በኋላ የተቀለበሰው የቀይ ካርድ ቅጣት በዓለም አቀፉ የእግር ኳስ የበላይ አካል ላይ ከባድ ተቃውሞ ቀስቅሶበታል።
ፊፋ የአሜሪካዊውን የቀይ ካርድ ቅጣት ማንሳቱ የእግር ኳስ ጨዋታ ተአማኒነትን አደጋ ላይ የሚጥል ነው በማለት የአውሮፓ አገራት የእግር ኳስ ፌዴሬሽን ዩኤፋ ተቃውሟል።
አሜሪካ ከቦሲኒያ ኤርዜጎቪና ጋር በነበራት ጨዋታ በፈጸመው ጥፋት በቀይ ካርድ የተሰናበተው አሜሪካዊ ተጫዋች ፎላሪን ባሎገን አገሩ ከቤልጂየም ጋር ማክሰኞ በምደታርገው የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ላይ መሰለፍ አይችልም ነበር።
ይህንን ውሳኔ የአውሮፓ እግር ኳስ ፌዴሬሽን “ያልታየ፣ ለመቀበል አስቸጋሪ እና ምክንያታዊ ያልሆነ” በማለት ፊፋ በውሳኔው ውስጥ ጣልቃ በመግባት ቅጣቱን ማገዱ “ቀይ መስመር ያለፈ” ነው ሲል ተችቶታል።
የዓለም እግር ኳስ የበላይ አካል የሆነው ፊፋ ለአሜሪካ ዋነኛ ግብ አስቆጣሪ በሆነው ተጫዋች ላይ የተላለፈውን የቀይ ካርድ ቅጣት ወዲያውኑ ተግባራዊ እንዳይሆን በማድረግ በቀጣዩ ወሳኝ የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ላይ እንዲሳተፍ ዕድል ፈጥሮለታል።
በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር ሲቢኤስ ቴሌቪዥን እንዳረጋገጠው ተጫዋቹ በቀጣይ ግጥሚያ ላይ እንዲሰለፍ የሚያደርገው ውሳኔ የተሰማው ፕሬዝዳንት ትራምፕ ሐሙስ ዕለት ከፊፋው ፕሬዝዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ ጋር በስልክ ከተነጋገሩ በኋላ ነው።
ከዚያም በኋላ እሁድ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ትልቅ ኢፍትሐዊነት” ያሉት የቀይ ካርድ ቅጣት “በመቀልበሱ” ፊፋን አመስግነዋል።
ማክሰኞ ከአሜሪካ ጋር የሚገጥመው የቤልጂየም እግር ኳስ ማኅበር የፊፋን ውሳኔ ተከትሎ ባወጣው መግለጫ አሜሪካዊው ተጫዋች በቀጣይ ግጥሚያ ላይ እንዲሳተፍ በመፈቀዱ “መገረሙን” ገልጿል።
የቤልጂየም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማክሲም ፕሪቮት “ለዚህ ተቀባይነት ለሌለው ውሳኔ ስልክ መደወል ምክንያት ከሆነ፣ የእግር ኳስን እና የስፖርትን መሠረታዊ ደንብን በግልጽ መጣስ ነው” በማለት ተቃውመዋል።
ከሙስና ጋር በተያያዘ በአሁኑ የፊፋ ፕሬዝዳንት ኢንፋንቲኖ ከ10 ዓመት በፊት የተተኩት ሴፕ ብላተር በኤክስ ላይ ጉዳዩን በተመለከተ “እግር ኳስ የፖለቲካ ኃይል የመጫወቻ ሜዳ ፈጽሞ መሆን የለበትም” ሲሉ ጽፈዋል።
የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር አንድ ተጫዋች ቀይ ካርድ ሲያገኝ ቀጣይ ጨዋታ ላይ እንዳይሰለፍ የሚጣለው ቅጣት “በፍላጎት የሚፈጸም ምርጫ ሳይሆን ደንብን መሠረት ደያረገ መርኅ ነው” ብሏል።
የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር እና ፊፋ ባለፉት ወራት በበርካታ ጉዳዮች ሲወዛገቡ የቆዩ ሲሆን፣ ሶማሊያዊው ዳኛ ወደ አሜሪካ እንዳይገባ ሲከለከል ማኅበሩ ተቃውሞውን ለማሳየት ዳኛው የአውሮፓ ጨዋታን እንዲዳኝ ጋብዞታል።